08/05/2026
አንበሳ ባንክ ከወለድ ነፃ የባንክ አገልግሎት የሼሪዓ አማካሪ ቦርድ አባላቱን አስተዋወቀ
===============================
አንበሳ ባንክ በሼሪዓ መርሆች ላይ ተመስርቶ የሚሰጠውን ከወለድ ነፃ የባንክ አገልግሎት የአስተዳደር ስርዓት የተደራጀ እንዲሆን እና አገልግሎቶቹ መሰረታዊ የሸሪዓ መርሆችን ያከበሩ እንዲሆኑ ለማስቻል የሼሪዓ አማካሪ ቦርድ ያቋቋመ ሲሆን የአማካሪ ቦርድ አባላቱን ከባንኩ የዲሬክተሮች ቦርድ እና የስራ አስፈጻሚ ቦርድ አባላት ጋር የማስተዋወቅ መርኃ ግብር ተካሂዷል፡፡
የሼሪዓ አማካሪ ቦርድ አባላቱ ሸይኽ አደም አብዱልቃድር - የትግራይ እስልምና ጉዳዮች ጠቅላይ ምክር ቤት ፕሬዝደንት፣ ሸይኽ ሙባረክ መሐመድ አወል - የፌዴራል ሸሪዓ ጠቅላይ ፍርድ ቤት ፕሬዝዳንት እና አቶ ኢብራሂም ዳውድ ሙዜይን - የፓን አፍሪካ የሸሪዓ አማካሪ ማህበር የምስራቅ አፍሪካ ተወካይ ሲሆኑ አባላቱ በእስልምና እምነት እና በሼሪዓ መርሆች ከፍተኛ ስፍራ ያለቸው፣ ከበሬታን እና አንቱታን ያተረፉ የኃይማኖች አባቶች ናቸው፡፡
የቦርድ አባላቱ የተመረጡት በእስልምና፣ በሸሪዓ ህግ፣ በሕግ ዳኝነት እንዲሁም ከወለድ ነፃ የባንክ አሰራር ዙሪያ ባላቸው ሰፊ ልምድ እና እውቀት መሰረት እንዲሁም በእስልምና ኃይማኖት ተቋማት ውስጥ ባላቸው ጠንካራ የአመራር ብቃት እና በማህበረሰቡ ዘንድ ባላቸው ከፍተኛ ተቀባይነት መሰረት መሆኑ በመርሃ ግብሩ ላይ ተገልጿል፡፡
አማካሪዎቹ የአንበሳ ባንክ ከወለድ ነፃ የባንክ አገልግሎቶች ከሸሪዓ መርሆዎች ጋር የተጣጣሙ፣ ግልፅ እና ታማኝ መሆናቸውን በመገምገም የተሻለ ሃሳብ የሚሰጡ ሲሆን ባንኩም ተወዳዳሪ እና ተገልጋዩን ህብረተሰብ የሚጠቅሙ አገልግሎቶችን ማቅረብ እንዲችል በማድረግ ከፍተኛ አስተዋጽዖ ይኖራቸዋል፡፡
አንበሳ ባንክ
እንጀምረው!
#እንጀምረው