23/01/2026
(ዘ-ሐበሻ ዜና) በኢትዮጵያ ግዙፍ የሆኑ የመንገድ እና የህንጻ ፕሮጀክቶችን በመገንባት የሚታወቀው የቻይና ኮሚኒኬሽን ኮንስትራክሽን ካምፓኒ (CCCC)፣ በድርጅቱ ውስጥ የሚሰሩ 8 ቻይናውያን ጥንዶችን በአዲስ አበባ ከተማ በድምቀት ዳረ።
ባለፈው ሰኞ ጃንዋሪ 19 በተካሄደው እና "ፍቅር በአህጉራት" (Love Across Continents) በተሰኘው በዚህ ልዩ ሥነ-ሥርዓት ላይ፣ ጥንዶቹ ቤተሰቦቻቸውን እና ወዳጅ ዘመዶቻቸውን ወክለው በተገኙ የሥራ ባልደረቦቻቸው ታጅበው የጋብቻ ቃል ኪዳን አስረዋል።
ኩባንያው (CCCC) ይህንን ዓይነት የጋራ የሰርግ ሥነ-ሥርዓት ሲያዘጋጅ ይህ ለአምስተኛ ጊዜ ነው። ድርጅቱ በየዓመቱ ጥር ወርን በመጠበቅ፣ ከትውልድ ሀገራቸው ርቀው በኢትዮጵያ ልማት ላይ እየተሳተፉ ለሚገኙ ሰራተኞቹ እንዲህ ዓይነት ማህበራዊ መድረክ ማዘጋጀቱ እንደ ባህል ተይዟል። ይህም የሰራተኞችን የስነ-ልቦና ጥንካሬ ከመገንባት ባለፈ፣ በሁለቱ ሀገራት ህዝቦች መካከል ያለውን የባህል ትስስር እንደሚያጠናክር ይታመናል።
በኢትዮጵያ የቻይና ኤምባሲ በማህበራዊ ትስስር ገጹ እንዳስታወቀው፣ የሙሽሮቹ ፈገግታ ለትዳር አጋሮቻቸው ያላቸውን ፍቅር ብቻ ሳይሆን፣ ለኢትዮጵያ ምድር ያላቸውን ክብር እና ፍቅር የሚያንፀባርቅ ነበር።
CCCC በኢትዮጵያ እንደ አዲስ አበባ-አዳማ የፍጥነት መንገድ፣ የወዳጅነት ፓርክ እና ሌሎች ቁልፍ መሰረተ ልማቶችን የገነባ ግዙፍ ተቋም ሲሆን፣ ይህ ዓመታዊ የሰርግ ዝግጅት የኩባንያው የውስጥ ማህበረሰብ ግንባታ (ኮርፖሬት ካልቸር) አንዱ አካል ሆኖ ቀጥሏል።