08/05/2026
ወደ ፊፋ 2026 የዓለም ዋንጫ ለሚያቀኑ ባለዕድለኞች የእንኳን ደስ አላችሁ መርሐ ግብር ተካሄደ፡፡
• ቪዛ ከኢትዮጵያ ንግድ ባንክ ጋር ያለውን የሥራ አጋርነት አጠናክሮ እንደሚቀጥል አስታወቀ፡፡
******************
የኢትዮጵያ ንግድ ባንክ እና ቪዛ በጋራ በመሆን በሲቢኢ ቪዛ ካርድ ተጠቅመው ክፍያ ለሚፈጽሙ ደንበኞች ባዘጋጁት የፊፋ 2026 ዓለም ዋንጫን መታደም የሚያስችል ዕድል አሸናፊ ለሆኑ ደንበኞች በባንኩ ዋና መሥሪያ ቤት የእንኳን ደስ አላችሁ መርሐ ግብር ተካሂዷል።
የባንካችን የቢዝነስ ኤክስኪዩቲቭ ምክትል ፕሬዚዳንት አቶ ደረጀ ፉፋ እና የዲጂታል ባንኪንግ ምክትል ፕሬዚዳንት አቶ ሚደቅሳ ቶሎሳ በዋናው መሥሪያ ቤት በተዘጋጀው በዚህ መርሐ ግብር ላይ በመገኘት ባለዕድል ለሆኑት የባንካችን ደንበኞች አቶ ይሄነው ብርሃኔ (ከቦሌ ዲስትሪክት) እና አቶ ሀብታሙ ተፈራ (ከአዳማ ዲስትሪክት) የእንኳን ደስ አላችሁ መልእክት አስተላልፈዋል።
በቪዛ የምስራቅ አፍሪካ ክላስተር ኃላፊ እና በኢትዮጵያ ሥራ አስኪያጅ የሆኑት አቶ ያሬድ እንዳለ በተመሳሳይ ለባለዕድለኞቹ እንኳን ደስ ያላችሁ በማለት፣ ቪዛ ከኢትዮጵያ ንግድ ባንክ ጋር ያለው የቆየ የሥራ አጋርነት ተጠናክሮ እንደሚቀጥል ተናግረዋል፡፡
ባንኩ እየሰጠ ያለውን ዲጂታል የባንክ አገልግሎት በማድነቅ፣ የሽልማቱ አሸናፊ በመሆናቸው ከፍተኛ ደስታ እንደተሰማቸው የገለፁት ባለዕድለኞቹ ደንበኞች ከሚመርጡት አንድ ወዳጃቸው ጋር በዩናይትድ ስቴትስ፣ ካናዳ እና ሜክሲኮ አዘጋጅነት የሚካሄደው የ2026™ የፊፋ ዓለም ዋንጫ የምድብ ጨዋታዎችን ሙሉ ወጫቸው ተሸፍኖ የሚታደሙ ሲሆን የተለያዩ ተጨማሪ ሽልማቶችንም የሚያገኙ ይሆናል።