11/10/2021
ከሶስት ዓመታት በፊት በጥቂት ባለራዕዮች የተመሰረተው ላዚዮ ብድርና ቁጠባ ኅብረት ስራ ማህበር (ጥቁር ውሀ) ከዓመት ወደ ዓመት ከፍተኛ ዕድገትን እያስመዘገበ ይገኛል፡፡
በእነዚህ ዓመታት ውስጥ ማህበራችን በዋናነት በሶስት ግቦች ላይ ትኩረት በማድረግ ተንቀሳቅሷል፡፡
• የአባላትን ቁጥር ማሳደግ
• የማህበሩን የገንዘብ አቅም (Capital) ማሳደግ
• ለአባላት የብድር አገልግሎት መስጠት
በእነዚህ የትኩረት ነጥቦች ላይ የተለያዩ እንቅስቃሴዎች ሲደረጉ ቆይተው አሁን ላይ የማህበራችን አባላት ቁጥር 63 መድረስ ችሏል፡፡
የማህበሩ መንቀሳቀሻ የገንዘብ አቅም ከ1 ነጥብ 1 ሚሊዮን ብር በላይ የደረሰ ሲሆን፤ ይህም አምና ከነበረው የግማሽ ሚሊዮን ብር ጋር ሲነፃፀር አመርቂ ውጤት የተገኘበት ሆኗል፡፡
በአንድ ዓመት የሥራ አፈፃፀሙ ብቻ 28 የማህበሩ አባላትን የብድር ተጠቃሚ ማድረግ የቻለው ማህበሩ፤ ለአንድ ግለሰብ እስከ አንድ መቶ ሺህ (100,000) ብር የብድር አገልግሎት የመስጠት አቅም ፈጥሯል፡፡
ማህበራችን እስከ አሁን የተጓዘበት ሁኔታ ከዕቅድ በላይ ስኬት ያስመዘገበበት ሆኗል፡፡
አባላት የቁጠባ እና የአክስዮን ድርሻቸውን እያሳደጉ መምጣታቸው ትልቅ ውጤት እያስገኘ መሆኑ ሊሰመርበት ይገባል፡፡
የአባላት ተጠቃሚነት እየተረጋገጠ በመምጣቱ የቁጠባ እና ብድር ግንዛቤ ማደጉ ተስትውሏል፡፡
በቴክኖሎጂ የታገዘው የመረጃ ልውውጥ እና ፈጣን አገልግሎት የማህበራችን መለያ መሆኑ በጉልህ የታየ ነው፡፡
በዚያው መጠን ለወደፊቱ ፈጣን ጉዟችን እንቅፋት ሊሆኑ የሚችሉ እና በቶሎ ሊስተካከሉ የሚገቡ ክፍተቶች ተስተውለዋል፡፡
ወርሀዊ ቁጠባ ለማስገባት የሚታዩ መዘግየቶች፣ ዝቅተኛውን የቁጠባ መጠን እንደ ግዴታ በመውሰድ ቁጠባን አለማሳደግ፣ ቸልተኝነት እና የተነሳሽነት ማነስ ሊቀረፉ የሚገባቸው የአንዳንድ አባላት ድክመቶች ናቸው፡፡
ማህበራችን ከፊቱ በርካታ መልካም አጋጣሚዎች እየጠበቁት ሲሆን በያዝነው ዓመት በከፍተኛ ሁኔታ ውጤታማ ሊያደርገው የሚችል እና ተተግባሪ ዕቅድ በማዘጋጀት ወደ እንቅስቃሴ ገብቷል፡፡
ለዕቅዱ ስኬት የሚረዱ አንዳንድ የህገ ደንብ ማሻሻያዎችን ያደረገ ሲሆን አጠቃላይ ዕቅዶችን እና የተሸሻሉ ህገ ደንቦችን እንደ አስፈላጊነቱ በተከታታይ ጽሑፎች ለአባላት የምናሳውቅ ይሆናል፡፡
ወሰናችን አድማስ ጥግ አረማመዳችን በጋራ ነው!
ላዚዮ ብድርና ቁጠባ ኅብረት ስራ ማህበር
(ጥቁር ውሀ)